በረዳት ፕሮፌሰር አደም ካሚል
እንደ መግቢያ
አሰላሙ አለይኩም ወራህመቱላሂ ወበረካቱ የአል-ኢስላም መፅሄት ዝግጅት ክፍል አዘጋጆች እና የተከበራችሁ የመፅሄቷ አንባቢያን ….. ቀደም ሲል በዚሁ አምድ ላይ “አህባሾችና ስዉር አጀንዳዎቻቸዉ” በሚል ርዕስ የተፃፈዉን ፊቸር አንብቤዋለሁ። ፅሁፉ ከሞላ ጎደል በበቂ ደረጃ የአህባሽን ቡድን ታሪካዊ መሰረት ቁልጭ አድርጎ ከመረጃዎች ጋር በማስደገፍ በማቅረቡ ዛሬ ስለ አህባሽ ምንነት ተጨማሪ ማብራሪያ ለመፃፍ ብዕሬን አላነሳሁም። በኢስላማዊ ፕሬሶቻችን እስካሁን ያልተዳሰሰዉን አጀንዳ በማንሳት ለአንባቢያን በቂ ግንዛቤ ለማስጨበጥ በመፈለግ እንጂ!
ይኼዉም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ምናልባትም ከአምስት ወራት ወዲህ በአገራችንም ሆነ ከአገር ዉጪ የሚኖሩ ሙስሊም ኢትዮጵያንን እያነጋገረ የሚገኘዉ የአህባሽ ቡድን በአሁኑ ወቅት የሚያደርገዉና እያደረገ ያለዉ እንቅስቃሴ አገራዊና አለምአቀፋዊ አንድምታዎች ምን ገጽታዎች እንዳላቸው መመልከቱ አስፈላጊ መሆኑን በማመኔ ነዉ። ይህን ሀሳብ ለማብራራት ወቅታዊና ነባራዊ መረጃዎችን እያጣቀስኩ ለመፃፍ ያነሳሳኝ ጉዳይ ቀደም ሲል በመፅሄቷ አጀንዳችን አምድ የሰፈረዉን ፅሁፍ ዓለም አቀፋዊና አገራዊ ትርጉም እና አንድምታዉን ባለመተንተኑ ሲሆን ፤ይህ መሰረታዊ ጉዳይ የብዙዎቻችን ሙስሊሞች ጥያቄ እንደሚሆን በማመን ያለኝን ዕዉቀት ወይም መረጃ የማካፈል ህዝባዊ ሀላፊነት በመጠኑም ቢሆን ለመወጣት ጭምር መሆኑን ተረዱኝ።
በተጨማሪም ይህን ፅሁፍ የሚያነቡ የአል-ኢስላም አጀንዳችን አምድ አንባቢያን እንዲገነዘቡልኝ የምፈልገዉ ነጥብ በአገራችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለያዩ መድረኮች በኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅለይ ምክር ቤት አስፈፃሚነት እና በኢፌድሪ መንግስት በተለይም በፌደራል ጉዳዩች ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ተባባሪነት ከሊባኖስ በመጡ የአህባሽ ቡድን መሪዎች አማካኝነት እየተሰጠ የሚገኘዉን ስልጠና ተከትሎ በአገራችን ሙስሊም ማህበረሰብ ዘንድ የአመለካከት እና የእምነት መከፋፈል ሳይሆን የእርስ በርስ ወንድማማችነትና አንድነት እንዲጠናከር ከማድረግ አንፃር የቡድኑን ወቅታዊ እንቅስቃሴ ከዓለም አቀፋዊ ክስተቶችና ከተጨባጭ አገራዊ ሁኔታዎቻችን ጋር እያገናዘቡ መመልከት ጠቀሜታዉ የጎላ መሆኑን በማመን ካለኝ የንባብ እና የጥናት ምርምር ሥራዎቼ መረጃዎችን በማጣቀስ ፅሁፉን ላዘጋጅ የመቻሌን ጉዳይ ነዉ ። ከዚሁ ጋር በተለይ በስልጠናዉ ሂደት መጅሊስን ወይም መንግስትን ለመክሰስ ሳይሆን ለማስገንዘብ፣ ለመዉቀስ ሳይሆን ለመማማር፣ለመተቸት ሳይሆን መረጃ ለመስጠት ወይም ለመለዋወጥ ይጠቅማል ከሚል ቀና አመለካከት ተነስቼ እንደፃፍኩ ለመጠቆም እወዳለሁ። ከዚህም በላይ በቡድን አመለካከቶች እየተምታታ የሚገኘዉ ሰፊዉ የኢትዮጵያ ሙስሊም ማህበረሰብ ስለ ቡድኑ እና ወቅታዊ እንቅስቃሴዎቹ አስፈላጊነት ዙሪያ የመረጃ ጥማቱን በመጠኑም ቢሆን ለማስታገስ ይህ ፅሁፍ የበኩሉን አዎንታዊ ሚና ይጫወታል ከሚል እሳቤ ተነስቼ መፃፌን ማስረዳት ተገቢ ይመስለኛል።
ወደ ርዕሰ ጉዳዩ ልመለስና በዚህ ወቅት የአህባሽ ቡድን በአገራችን አመለካቱና እምነቱን ለማስረፅ እንዴት ፈለገ ? ወይም የአህባሽ አመለካከት በኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች ዘንድ ተቀባይነት እንዲያገኝ ለምን ተፈለገ ? ለሚለዉ የብዙሃኑ ኢትዮጵያዊ ሙስሊም ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ልሞክር… ከዓለም አቀፋዊ ነባራዊና ወቅታዊ ክስተቶች አንፃር የአህባሽ ቡድን የሚኖረዉን አንድምታ በመተንተን ልጀምር ……
የቡድኑ አመለካከት እና ዓለም አቀፋዊ ገፅታዎች
በዓለም አቀፍ ደረጃ የሶሻሊስት ርዕዮተ አለም አመለካከት ከፈራረሰ በኋላ በተለይም በምንገኝበት ዘመን የዓለም ማህበረሰብ በግሎባላይዜሽን ጥላ ስር እንዲሰባሰብ ብሎም የአንድ ባህል ፤ወግና ልምድ አራማጅ እንዲሆን ወይም በአንድ ማህበረሰባዊ ኢኮኖሚ (social economy) ሥርአት እንዲመራ የሚለዉ የፖለቲከኞች አመለካከት የበላይነቱን ይዞ ይገኛል። በሆላንድ ዋና ከተማ ሄልሲንኪ በተካሄደዉ ስብሰባ እነማርክ ዴክፓርቸርና እነ ኒክሰንን ጨምሮ ሌሎችም ታላላቅ የፖለቲካ ሊቃዉንት አማካኝነት የተነደፈዉ ይህ ዕቅድም ሰፊ ተቀባይነት አግኝቷል ።ይሁንና ዕቅዱን ለማሳካት ከፊትለፊት ያለዉ አስቸጋሪው ፈተና ከእስልምና ሃይማኖት መስፋፋትና መጠናከር ጋር የተያያዘ አድርገዉ ይመለከቱታል። ከ15 ዓመታት በኋላ እንደ ሶሻሊስት በቀላሉ የሚመታ ሃይመኖት አለመሆኑን የተገነዘቡት እነዚሁ ምዕራባዊያን ፖለቲከኞች ታዲያ ሀይማኖቱ በተዘዋዋሪ መንገድ የሚከፋፈልበትን ስትራቴጂክ ስልት የመጠቀም ዘመቻቸዉን በሰፊው እያካሄዱ ይገኛሉ። በአሁኑ ወቅት የሀይማኖቱን ዓለም አቀፋዊ አንድነት ለማዳከም እየጣሩ ያሉት፤ በዓለም አቀፋዊ ደረጃ በተለያዩ ክፍለ አህጉራት እየተከሰቱ ያሉት ፖለቲካዊ ፣ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ የሚሰጠዉ የእስልምና ሀይማኖት አስተምሮቶች መሆናቸዉን በጊዜ ሂደት እየተገነዘቡ በመምጣታቸው ነዉ። ከምዕራባዉያኑ መካከል ጥቂት የማይባሉት ምሁራን ፣የፖለቲካና የተለያዩ አይዶሎጂዎችን እያራመዱ የሚገኙት እነዚሁ ወገኖች ይህንኑ እየተገነዘቡ ከመምጣታቸዉም በላይ እስልምና ለአለም ህዝቦች ሁሉ ተስማሚ ሀይማኖት መሆኑን በተለያዩ መንገዶች ማረጋገጣቸዉ ለፀረ ኢስላም ተዋናያኑና የፖለቲካ ሰዎች ትልቅ ራስ ምታት ሆኗል። በተለይ ደግሞ ለእስራኤላዉያኑ!
የዓረቡን ዓለም ክስተት ተከትሎ ያለው ስጋት
በመካከለኛዉ ምስራቅ ካለፉት አስር ወራት ወዲህ ያገረሸዉ ህዝባዊ አመፅ እስራኤላውያኑን እረፍት ነስቷቸዋል። በተለይም የመካከለኛዉ ምስራቅ አረብ ሀገራት ህዝቦች በመሪዎቻቸዉ ላይ ያላቸዉ አመኔታ እየመነመነ መምጣቱ እና ይህንንም ተከታሎም ለእስራኤል ታማኝ የሚባሉ መሪዎቻቸዉ ከስልጣናቸዉ እየወረዱ በመሆኑ እስልምናን ለማተራመስ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ምክንያት ሆኗቸዋል። ይህ የቀጠናዉ አገራት የለዉጥና የነዉጥ ማዕበል ለእስራኤላውያን በጣም አስጊ ሆኖ ይታያል ። በአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴርም ሆነ በሌሎች አማካሪዎች እስራኤላውያን የራሳቸዉን ቤት እንደገና እንደ አዲስ ዕቅድ ነድፈዉ እንዲሰሩ ባሳሰቧቸዉ መሰረት የእስራኤል መሪዎች ወደ ፊት ከዓረቡ አለም ህዝቦች ጋር ስምምነትና ድርድሮችን ማድረግ የማይችሉበት ሁኔታ ይፈጥራል የሚል ስጋት አይሎባቸዉ ይታያሉ። በዚህም ከፍተኛ ዉጥረትና ጭንቀት ነግሶባቸዋል።
ኢትዮጵያም የስጋታቸዉ አካል ትሆን?
እስራኤሎች ኢትዮጵያን ከዐረቡ ዐለም ጋር ባላት ታሪካዊ ትስስር አንፃርም ሆነ በጂኦግራፊያዊ አቀማመጧ ስትራቴጂያዊነት ሳቢያ ከዐረቡ ዓለም አገራት ለይተዉ አይመለከቷትም። በተጨማሪም በርካታ ህዝብ ቁጥር ያለዉ ኢትዮጵያዊ የእስልምና ሓይማኖት ተከታይ በመሆኑ ከአፍሪካ ቀንድ ሀገሮች በግንባር ቀደምነት ራስ ምታት የሆነችባቸዉ ይመስላል። ስለሆነም እስራኤል የዐረቡ ዓለም የለዉጥና የነዉጥ ማዕበል ወደ ኢትዮጵያ እንዳይደርስ ያላትን ፍላጎት ለማንፀባረቅ ስትል ከተጠቀመችባቸዉ ስትራቴጂክ ዕቅድ አንዱና ዋነኛዉ የአህባሽ ቡድንን አመለካከትና አስተምሮት በኢትዮጵያዉያኑ ሙስሊሞች ላይ የማስረፅ ዘመቻዋ ነዉ። ምክንያቱም የአህባሽ አመለካከት ከእስራኤላዉያን አመለካከት ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ነዉና!።
ዩቲዩብ፣ ፌስቡክ፣ ቲዉተር…የስጋት አካል ሆነዋል
ዓለምን ወደ መንደርነት ያቀራረበው የዘመናችን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ስርፀት ህዝብን ለአንድ አላማ ለማሰለፍ አመቺ ሆኗል። እናም እንደ ፌስቡክ እና ቲዉተር የመሳሰሉ የመልዕክት ማስተላለፊያ ዘዴዎች ለእስራኤላዉያኑ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ስጋት መሆናቸዉ አልቀረም። ለምሳሌ እ.ኤ.አ ኦክተበር 15/2011 ብቻ ከስፔን፣ ስኮትላንድ ፣ጣልያንና አሜሪካን የዘለቀዉ ህዝባዊ ሰልፍ በ82 አገሮች 1 ሺ ከተሞች የሚኖሩ ህዝቦች ሃይማኖት፣ ዘር፣ ብሄርና ጎሳ ሳይለያቸዉ ለአንድ ዓላማ ወደ አደባባይ እንዲወጡ ለማድረግ እነዚሁ የመልዕክት ማስተላለፊያ ቴክኖሎጂዎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ማስታወስ ይቻላል። እነዚህን ህዝቦች መቀስቀስ የተቻለዉ በዘመኑ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፍሬዎች መሆኑ ታዲያ ለእስራኤላዉያን ተዘዋዋሪ የስጋት ደዉል እንዲያቃጭልባቸዉ ምክኒያት ሆኗል። በተጨማሪም የሙስሊሙና ዐረቡ ዓለም ሕዝባዊ ንቅናቄ በእነዚህ የቴክኖሎጂ ዉጤቶች ጭምር የታገዘ መሆኑ ታዲያ ለእስራኤል ዘመን ያልሻረዉና የማይሽረዉ ስጋት አከናንቧታል።
ከዚሁ ጋር በተያያዘ በአሁኑ ወቅት በዓለም ሃያላን አገራት ጭምር ለተከሰተዉ የኢኮኖሚ ቀዉስ እስልምና እንደ መፍትሄ እየተወሰደ መምጣቱ ለእስራኤላዉያንና ፀረ-ኢስላም እይታ ባላቸዉ ምዕራባዉያን የሙስሊምን ህዝብ እምነትና አመለካከት አቅጣጫ ለማስቀየር መባዘናቸዉን ተያይዘዉታል ።አጀንዳ ይዘዉና ዕቅድ ነድፈዉ ከሚንቀሳቀሱባቸዉ አቅጣጫ የማሳቻ ዘዴዎቻቸው መካከል ደግሞ ዋነኛዉ ስልት የአህባሽ ቡድንን አመለካከት የማስረፅ ሂደት ነዉ ።ይህ ነባራዊና ወቅታዊ ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች ናቸዉ እንግዲህ የአህባሽ ቡድን እንቅስቃሴ በአገራችን ጭምር ተጠናክሮ እንዲመጣ ምክንያት የሆነዉ ። የዚህ ቡድን በአገር ዉስጥ እንዲስተናገድ ምክኒያት የሆኑትን ነባራዊና ወቅታዊ ሁኔታዎች ደግሞ በመቀጠል ለመጥቀስ እሞክራለሁ።
አገር አቀፍ አንድምታዎች
የኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች በአፄዎቹ ዘመን በተለይ “በኢትዮጵያ የሚኖሩ ሙሰሊሞች” እየተባሉ ይጠሩበት በነበረበት ወቅት ከሀገራዊ የልማት እና የፖለቲካ አጀንዳዎች ተገልለዉ ኖረዋል። ከወታደራዊና ደህንነት ቦታዎች ርቀዋል። የመሪነት ሚና አልነበራቸዉም። ከዚህም በላይ የትምህርት ተሳትፏቸዉ እጅግ የመነመነ ከመባል ይልቅ ያልነበረ በሚባልበት ደረጃ ላይ ሆኖ ዘመናትን አሳልፈዋል። ባህልና እምነታቸዉን እየገበሩ የኖሩበት ያ ክፉ ዘመን ዛሬ ላይ የለም። በህዝቦች የአመታት ትግል ሁሉንም የአገሪቱን ዜጎች የሀይማኖት ተከታዮች በእኩልነት ደረጃ እና በጋራ የሚያስተናግድ ህገ መንግስታዊ ሥርዓት ዕዉን ሆኗልና! ይህንኑ ዴሞክራሲያዊ ስርአት ተከትሎ በተፈጠረዉ ምቹ ሁኔታ ኢትዮጲያዊነታቸዉ ተረጋግጦ የፌዴራሊዝም ሥርአቱ ተዋናይና ተጠቃሚ መሆን ጀምረዋል። ከክልል እስከ ፌዴራል መንግስት ባሉ መዋቅሮች እንደሌሎች እምነት ተከታዮች ሁሉ የልማት እና ፖለቲካ ተሳታፊነት እና ተጠቃሚነትን እያረጋገጡ መጥተዋል ።
ይሁንና ይህ የሙስሊሞች የተነቃቃ ተሳታፊነት እና ተጠቃሚነት ያልተዋጠላለቸዉ አንዳንድ የዉጭና የዉስጥ ሃይሎች ዛሬም ድረስ ለመኖራቸዉ አስረጂ መጥቀስ አያሻም። እነዚህ ሃይሎች ኢትዮጵያዊው ሙስሊም መማሩ፣ በልማት የመሳተፉ፣ ፖለቲካዊ ስልጣን መያዙ፣ በመንግስት የአስተዳደር የሲቪል ሰርቪስ መዋቅር መገኘቱ…ወዘተ ይከነክናቸዋል። ስሙን፣ ባህሉን፣ ወጉን፣ ልምዱን፣ ቅርሱን፣ መንፈሳዊና አገራዊ ማንነቱን እንዳይዝ፤ እዚህም እዚያም የሚያደርገዉ ሀገራዊ ተሳትፎ በእርግጥም ጥቂት የማይባሉትን የዉጪና የዉስጥ ሃይሎችን አሳስቧል። አስጨንቋልም! ይህንኑም ጭንቀት ለማርገብ የተያዘዉ አንዱ አማራጭ የተረጋጋና ሠላማዊ የኢትዮጲያ ሙስሊሞች ማህበረሰብ አንድነቱን ጠብቆ እንዳይቀጥልና እንዳይጠናከር የቤት ስራ መስጠት ነው። ለዚህ ደግሞ ከቅርብ ግዜ ወዲህ በአገራችን እየተስተናገደ ያለዉ የአህባሽ ቡድን እንቅስቃሴ በቂ ማሳያ ሊሆን ይችላል። ነዉም!!
አንዳንድ የዉጭና የዉስጥ ፀረ-ኢስላም ሃይሎች ያሳሰበዉ ጉዳይ የሙስሊሙ የተነቃቃ ተሳትፎ ብቻም አይደለም፤ በትክክለኛዉና በቅርቡ በተደረገዉ የቤቶችና ህዝብ ቆጠራ ዉጤት መሰረት የህዝበ ሙስሊሙ ቁጥር ከጠበቁት በላይ ገዝፎ የመዉጣቱ ጉዳይም ሌላዉ ጭንቀታቸዉ ሆኖ ይታያል። ከዚህ ፈጣን የህዝብ ቁጥር ዕድገት ጋር በተያያዘ ይህ ሙሰሊም ማህበረሰብ አንድነቱን ጠብቆ ከዘለቀና አሁን ካለዉ መንግስታዊ ስረዓት ጋር ተቀራርቦ ለሃገሩ ልማት ከሰራ ውሎ አድሮ ሠላም የሚነሳቸዉ ሃይሎች አይታጡም። ለአብነት ያህል በ1997ና በ2002 በተካሄዱት አገር አቀፍ ምርጫዎች ብዙሃኑ የአገሪቱ ሙስሊም ማህበረሰብ ኢህአዴግን በድምጹ መርጦኣል። ሙስሊሙ እንደ ትላንቱ ሁሉ ወደፊትም ለኢህአዴግ ድምጹን መስጥቱን ከቀጠለና አጋርነቱን ካረጋገጠ የእነዚህ እኩይ ሃይሎች ስጋት እጥፍ ድርብ መሆኑ አይቀሬ በመሆኑ ከወዲሁ በተለይም ከሶስት ዓመት በኋላ የሚካሄደው አምስተኛዉ ዙር ብሄራዊ ምርጫ ከመድረሱ አስቀድሞ መንግስትን ከህዝበ ሙስሊሙ ጋር ለማጋጨት ወይም ለማራራቅ የሚረዱ ስራዎችን ለመስራት ቀን ከሌት እየደከሙ ይገኛሉ ። በቀጣዩ ምርጫ ሙስሊሙ ለኢህአዴግ ድምፅ የሚሰጥበትን ዕድል ለማኮላሸት የሚደረግ ፅኑ እንቅስቃሴ መታየት በቂ ማስረጃ ሆኖም ይታያል ። እናም “አህባሽ ” የሚለዉ እምነት እና አመለካከት በኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች ላይ ለማንሰራፋት የተጀመረዉ ዘመቻ ከላይ በተጠቀሱትና በግልፅ ባልተነገሩት ስዉር አጀንዳ አራማጆች ግፊትና ጫና ምክንያት ስለመመንጨቱ መገንዘብ አያዳጋትም።
ህዝበ ሙስሊሙን ከመንግስት ጋር ያለዉን መልካም ግንኙነት ለማበላሸት እና ሙስሊሙ መንግስትን ፤ መንግስት ደግሞ ብዙሃኑን ሙስሊም እንዲሸሸ የሚያደርጉ የዉጪና የዉስጥ ሃይሎች መኖራቸዉን ዘንግተዉ የአህባሽን እንቅስቃሴ የሚያስተናግዱና በተለይም እየተሳተፉና ድጋፍ እየሰጡ ያሉ ጥቂት የመንግስት አስፈፃሚ አካላት ሊከተል የሚችለዉን አሉታዊ ችግር ተገንዝበዉ ይሆን? ወይስ ያሳሳታቸዉና እያሳሳታቸዉ የሚገኝዉን ሃይል በማወቅም ሆነ ብለማወቅ አልተገነዘቡም? የሆነ ሆኖ እነዚህ መሰረታዊ ጥያቄዎችን ቆም ብሎ እጅግ በሰከነ መንፈስ ማስተዋልና መፈተሹ ተገቢም ወቅታዊም ይመስላል።
እንደ መሸጋገሪያ
አህባሾች ከእስራኤል ጋር ያላቸዉ ግንኙነት ቀደም ሲል “አህባሾች እና ስዉር አጀንዳዎቻቸዉ” ፅሁፍ ላይ ያልተጠቀሰዉ የቡድኑ መስራች አብደላ አል ሃረሪ ቀደም ሲል ሊባኖስ ከመሄዱ በፊት በሃረር በፈጠረዉ ዉዝግብ በርካታ ኡለሞች ከሃገር እንዲወጡ ያደረገዉ ከአፄ ሃይለስላሴ ገዢ መደብ ጋር በመመሳጠር እነደነበር ነዉ። በኡለሞች ላይ ያደረሰዉ አሰቃቂ ግፍ እና በደል ዓይነቱ ብዙ ነበር ። እርሱ ያስከተለዉ የዚህ ችግር ገፈት ቀማሽ የሆኑ ዑለሞች ዛሬም ድረስ እዚሁ በአገራችን በህይወት አሉና ዝርዝሩን እነርሱ እንዲናገሩ እንተዉላቸዉ። ከአይሁድ ጋር ስለነበረው ግንኙነት ትንሽ ነገር ለማለት ያህል፤ አብደላ አልሃሪሪ በግብፅ፣ በሶሪያና በእስራኤል ባደረገዉ እንቅስቃሴ ተልዕኮዉን ለመፈፀም አመቺ መድረክ አላገኘም ነበር ። በወቅቱ የ17 ዓመት ጦርነትን ያስተናገደችዉ ሊባኖስ ግን ዋነኛ መድረክ ሆነዋለች። በወቅቱ ሊባኖስ የብዙ ጎሳዎች መኖሪያና በእርስ በርስ ጦርነት የደቀቀች አገር ከመሆኗም በላይ እንደ ሺዓ፣ ሱንይ፣ ዴርዚነና እና ሌሎችም አመለካከቶችን የሚያራምዱ ህዝቦችን በግጭት ስታስታምም የኖረች ሃገር ነች ። በአሁኑ ወቅትም ይህ ሁኔታ በጠራ ሁኔታ ላይ አለመገኘቱ እንዳለ ሆኖ አንድም ጊዜ ሠላምና መረጋጋት ያልታየበት ሆና ቆይታለች። የሊባኖስ የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስተር ሱንይ ነበር ። የፓርላማዉ አፈ ጉባኤ ሺአ የነበረ ሲሆን፤ ፕሬዘዳንቱ ደግሞ ክርስቲያን ሆኖ እናገኘዋለን … የሆነ ሆኖ አብደላ አልሃሪሪ እንቁላሉን እንዲህ ዓይነት ታሪካዊ ስዕል በነበራትና ባላት ሊባኖስ ነው የጣለው፡፡ በወቅቱ በአመለካከቱ ያጠመቃቸውን የፓርላማ አባላት እስከ ማፍራትም ደርሷል፡፡ በነገራችን ላይ አብደላህ አልሃራሪ እ.ኤ.አ. በ1982 በሊባኖስና በእስራኤሎች መካከል በተካሄደው ጦርነት ከሞሳድ ጋር በመተባበር የመረጃ ምንጭ ሆኖ ለእስራኤሎች ሲያገለግል የነበረ ነው፡፡ ይህ እስራኤል ጋር ምን ያህል የጠበቀ ቁርኝነት እንዳለው አመላካች ነው፡፡ እንዲያውም በአንድ ወቅት በሰጠው ብይን (ኢፍታዕ) ነብዩ መሐመድ (ሠ.ዐ.ወ.) ከመካ መዲና የሸሹት አቅሙና መሰባሰቡ ያለው ሰራዊት ስላለነበራቸውና ሰራዊቱ ደካማ ስለለበር እንዲሆነ ፣ ስደቱን ያካሄዱት ለእምነታቸው ሲሉ መሆኑን በማብራራት ፍልስጤሞች ከጋዛም ይሁን ከሌላ ጋር ሆነው እስራኤልን በመልቀቅ ወደ ሌሎች ኢስላማዊ አገራት መስደድ እንዳለባቸው ሲናገር… በብዙሃኑ እስራኤላውያን ዘንድ ከፍተኛ የሆነ አድናቆትን አግኝቷል፡፡ ከዚህ ዝና መቸር ባለፈም ተቀባይነትን አግኝቷል፡፡ እስራኤሎች ታዲያ ዛሬም ድረስ የአህባሽ አመለካከትና አስተሳሰብ እንዲስፋፋ እየሰሩ የሚገኙት በዚሁ ምክንያት መሆኑን መገንዘብና ማስተንተን ጠቃሚ ነው፡፡
ከሊባኖስ የመጡ አስተማሪዎች እንዴት ይታመናሉ?
የአህባሽን አመለካከት ለማስረፅ ሲባል ወደ ኢትዮጵያ የመጡት ሊባኖሳዊያን መምህራን እንዴት ይታመናሉ ያልኩት ያለምክንያት አይደለም፡፡ ሊባኖሳውያን በባህሪያቸው እንደመምህር ወይም እንደ መልካም ምሳሌ ተደርገው ስለማይወሰዱ እንጂ! እነዚህ ዜጎች ለኢትዮዽያውያን እንደማይበጁ የአደባባይ ሚስጥር ነው! ጥሩ ምሳሌ ልጥቀስ… ወደአገራቸው ለሥራ የሄዱ ኢትጵያውያን ላይ እየፈፀሙት ያለውና ለዘመናት ሲፈፅሙባቸው የኖሩት በደልና ስቃይ ዛሬም ድረስ ቀጥሏል፡፡ ለሀበሻ (ለኢትዮጵያውያን) ያላቸው ሰብዓዊ ክብርና ደረጃ የዘቀጠ መሆኑን በቅጥረኛ ሰራኞቻችን ላይ የሚፈፀሙት አረመናዊ ድርጊት ከበቂ በላይ ማስረጃ ነው፡፡ በስቃይ በትራቸው ህይወቷ ያለፈችውን እህታችንንት አስክሬን በክብር ከመላክ ይልቅ የሰውነት አካሏን እየበለቱ የሚያወጡ ናቸው። ግብረገብነት ይሌላቸው፣ ለማህበረሰብ የማያስቡ አረመናዊ በትራቸው የሚበረታ ከሊባኖሳውያን ዜጎች ምን መማር ይቻለናል? ለዚያውም ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችን እንዴት ሊያስተምሩ ይችላሉ? እናም ዛሬ የመጡልንን ሊባኖሳዊያን አስተማሪዎች እንዴት እንመን! በቅርቡ ከማዳስካር ወደ ሊባኖስ ከሄዱ 85 ሰራተኞች መካከል በአንዷ ላይ የፈፀሙት ግፍ የአገሪቱ መንግስት ን በ24 ሰዓታት ቀሪ ዜጎቹን ከሊባኖስ ለማስወጣት አስገድዶታል። በእኛ ኢትዮጵያውያኑ ቅጥረኞች ላይ ግን ለዓመታት በደል ሲፈፅሙ ከኖሩት ሊባኖሳውያን ዜጎቻችንን መታደግ ተስኖን መኖራችን እያንገበገበን ጭራሽ እነርሱኑ እንዲያስተምሩን የጋበዙልን እነማን ይሆኑ? እንደ እኔ በጥቅሉ ከሊባኖሳውያን መልካም አስተምህሮት ይመጣል ብሎ መጠበቅ ከየዋህነትም በላይ ጅልነት ነው፡፡
ይልቁንም የአገራችን ኡለሞች ለሌሎች የተትረፈረፈ ዕውቀት አላቸው። ለምሳሌ በሳውዲ ታላላቅ ቦታዎች የማስተማር ልምድ ያካበቱ ታዋቂ ምሁራኖች ሞልተውናል፡፡ ከውጪ ማምጣቱ አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘስ እነሱዳንና ግብፅ ለም እንደተዘነጉ በራሱ የሚገርም ትዝብትን ያተርፋል። ከእነዚህ ጎረቤት አገራት ምሁራን ቢመጡ በባህልም ሆነ በጂኦግራያዊ አቀማመጥ ተመሳሳይነት ስላላቸው ከኢትዮዽያውያን ሙስሊሞች ጋር የተሻለ መቀራረብና መተማመን ስለሚኖራቸው ጥሩ በተማርንባቸው ነበር። ከዚህም በላይ ለሀበሻ ያላቸውን ክብር ባየን ምንኛ መልካም ነበር እያልኩ ወደ አህባሾች ስልጠና መድረኮችና አንደምታዎቻቸው ልሸጋገር፡፡
የስልጠና መድረኮቹን በወፍ በረር
የስልጠና መድረኮች (ወሃብያን) ለመዋጋት እንደተዘጋጁ የመነገሩ ጉዳይ ብዙሃኑን ግራ ያጋባ ከመሆኑም በላይ የቃሉ ምንነት እና የትኛዉን አካል ለማመላከት ጥቅም ላይ እንደዋለ ግልፅ አይደለም ። በመሰረቱ “ወሃብያ” እንደ አመለካከት ተይዞ ከሆነ ቃሉ ምን እንደሆነ ተናጋሪዎቹ በዉል የተገነዘቡት አይመስለኝም። በነገራችን ላይ ወሃብያ የመሀመድ ኢብኑ አብዱልወሃብ ስም ነዉ። ከ1703 እስከ 1791 እ.ኤ.አ ደዕያ በተባለችዉና በሳዑዲ አረቢያ አካባቢ የሚኖር የነበረ የአካባቢዉ ማህበረሰብ ሃይማኖታዊ መሪ የነበረ ግለሰብ መጠሪያ ስም እንጂ የሌላ ወካይና ገላጭ ቃል አለመሆኑን ሊታወቅ ይገባል። በወቅቱ እርሱ በሚኖርበት ዘመንና ቦታ ይኖሩ የነበሩ ህዝቦች ያካሂዱት የነበረዉን የጣዖት አምልኮ እንዲተዉ ያስተምርና ይታገል የነበረ ሰዉ ነዉ። ተዉሂድን የማስተማር እንቅስቃሴዉም ከፍተኛ የነበረና (መፅሃፍ በመፃፍ ጭምር ) ባደርገዉ የማስተማር ተሳትፎው ታዋቂነትን ያተረፈ ሰዉ እንደሆነ ከታሪክ ድርሳናት እንረዳለን። ከዚህ ዉጪ ግን በሌላዉ ላይ ጦር የሰበቀ ግለሰብ አልነበረም ። ከሞተ ሰዉና ጣኦት አምላኪነት ህብረተሰቡ እንዲላቀቅ ባካሄደዉ የማስተማር ዘመቻ ማንንም አልገደለም። በጥቅሉ ወሃብያ የሚለዉ መጠሪያ የዚህ ሰዉ ስም ከመሆን የዘለለ መገለጫ ሊኖረዉ እንደማይችል መገንዘብ ተገቢ ይመስለኛል ።
ሌላዉ በስልጠናዉ መድረኮች በተለይም በባህርዳር አካባቢ በተዘጋጁ መድረኮች ላይ በስፋት ወሃብያን እና የሳዑዲ ዓረቢያን ንጉሳዊ አገዛዝ እና ዜጎች ከ“ወሃብያ” ጋር የማስተሳሰር አዝማሚያዎች የመታየታቸዉ ጉዳይ ነዉ።
የሳዑዲ ዐረቢያ ህገ-መንግስት የተራቀቀዉ ቁረአንና ሃዲስን መሰረት አድርጎ እንጂ የወሃብያን ስርዓት መሰረት አያደርግም። ከዚሁ ጋር በተያያዘ ወሃብያን ከአልቃኢዳ ጋር የማቆራኘት አዝማሚያ በስፋት ተንፀባርቆ ነበር። እዉነታዉ ግን አልቃኢዳ የራሱ ዓላማ ያለዉ አሸባሪና አጥቂ ቡድን ሲሆን ሳዑዲ አረቢያም በዚህ አጥቂ ድርጅት በተደጋጋሚ የተጎዳች ሀገር ሆና እናገኛታለን ። በአልቃኢዳ የፈንጂ ጥቃቶች ሳቢያ አያሌ ንፁሃን ዜጎቿ አጥታለች ። ሃቁ ይህ ሆኖ እያለ ግን ወሃብያን ከአልቃኢዳ ጋር ማቀላቀል ታሪካዊ ጥፋት ነዉ። የስልጠና መድረኩ መሪዎች ወይም አሰልጣኞች ከዚሁ ጋር በተያያዘ ሳዑዲ አረቢያን እንደ ሃገርና እንደ ህዝብ ማዉገዛቸዉ በግልፅ ታይቷል። ይህ ምክንያቱ ደግሞ አንድና አንድ ነዉ። እሱም አብደላ አልሃረሪ ለሳዑዲ ትልቅ ጥላቻ ያለዉ ሰዉ ሰለነበር ነዉ። ጥላቻዉ የመነጨዉ ደግሞ ሳዑዲ ዐረቢያ በወቅቱ ሊባኖስ ከ17 ዓመት በኋላ በጧኢፍ ስምምነት መሰረት የእርስ በርስ የጎሳ ግጭቷ እንዲያቆምና ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍንባት ግንባር ቀደም ሚና በመጫወቷ ነዉ። አብደላ አልሃረሪ በወቅቱ ከጀርባዉ የነበረዉ የእስራኤልን ተልዕኮ ለማሳካት ይህ ሁኔታ አልፈቅድለት ስላለ ነው። በተጨማሪም ወደ ሠላም የመጡ የወቅቱ የሊባኖስ መሪዎች ስምምነቱን መቀበላቸዉ የሳዑዲ አረቢያን የሽምግልና ጥረት በበጎ ስለማይመለከተዉ ነበር።
ያም ሆነ ይህ በስልጠና መድረኮቹ ሳዑዲ ዓረቢያን እንደ አገርና እንደመንግስት ማዉገዙ በኢትዮ-ሳዑዲ የወደፊት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ዙሪያ መጥፎ ጥላ የሚያጠላ መሆኑ አይቀሬ ነዉ። በተለይ እንደተወገዙ ከሰሙ በሳዑዲ የሚኖሩ ከግማሽ ሚሊየን ያላነሱ ዜጎቻችንን “ከአገሬ ይዉጡ……” ብትል፤ ተጎጂዎቹ እኛዉ ነን። በዚህ ደግሞ ሀገርም መንግስትም ይጎዳሉ። ስለዚህ ይህችን አገር ማስኮረፍ ሊያስከትል የሚችለዉ ችግር ምን ሊሆን እንደሚችል ግንዛቤ የተወሰደበት አይመስለኝም።
ከዚህም ሌላ ለስልጠና መድረኮቹ ማስፈፀሚያ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ፈሰስ መደረጉ እና ስልጠናዉ ከሚያስገኘዉ ወጤት ወይም ለዉጥ ጋር ሲነፃፀር ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚያመዝን ይመስላል ። መጅሊሳችን ለስልጠናዉ ይህን ያህል ገንዘብ ከመንግስት ተደጉሞ ጭምር እኔዳወጣ በሠፊዉ ይነገራል። ይህን ከማድረግ ይልቅ በየጊዜዉ ለስደት የሚዳረጉትን የአርብቶ አደር እና አርሶ አደር ልጆች በስደት በየበረሃዉ እየወደቁ ፣በየባህሩ እየሰመጡ ከሚያልቁ እነዚህን ዜጎቻችንን ለመቋቋም ወይም በተለያዩ የስራ ፈጠራ ፕሮጀክቶች እነዲሳተፉ ቢያደረግና፤ በዚህም ራሳቸዉን እና አገራቸዉን እንዲጠቅሙ ከመንግስት ጋር ተባብሮ ቢሰራ ምነኛ ባማረበት ነበር!
ከዉጪ ፖሊሲያችን አኳያ አሉታዊ ተፅዕኖዎች
ኢትዮጵያችን በተለይም በአፄዎች ዘመን ታራምድ የነበረዉ የዉጪ ግንኙነት ፖሊሲ ትኩረት ከካፒታሊዝም አገራት ጠንካራ ግንኙነትን መመስረት ላይ አትኩሯል። በተለይ ደግሞ በዘመነ ደርግ ከዓረብ አገሮች ጋር ግንኙነታችን ሻክሮ የቆየና በተለያዩ መስኮች በትብብር አብሮ የመስራት ዕድሉ ዝግ ሆኖ የቆየበትን ሁኔታ እናስታዉሳለን። በአሁኑ ዴሞክራሲያዊ መንግስት ግን ግንኙነታችን በአዲስ ምዕራፍ የሚቀጥልበትንና በጋራ የምንሰራበትን ምቹ ሁኔታ የፈጠረ የዉጪ ግንኙነት ፖሊሲ ተቀርጾ ስራ ላይ ውሏል። በማንም አገር የዉስጥ ጉዳይ ላይ ጣልቃ ባለመግባት በጋራ ብሄራዊ ጥቅሞቻችንንና ፍላጎታችን ዙሪያ ተቀራርበንና ተፈቃቅደን መስራት የምንችልበት መርህን በሚከተለዉ የወቅቱ የዉጪ ግንኙነት ፖሊሲያችን አማካኝነት በተለይ ከሳዑዲ ዓረቢያ ጋር በኢኮኖሚ፣ በልማቱና ኢንቨስትመንቱ ዘርፍ በላቀ ደረጃ መጠቃቀም ይቻላል። እንዲሁም አገራችን ካላት የቆየ ኢስላማዊ ታሪካዊ አሻራዎች አንፃርም በቱሪዝም መስክ የተሻለ ግንኙነት ለመፍጠር ተችሏል። ይሁንና ይህ ግንኙነታችን ያልተዋጠላቸዉ አንዳንድ የዉጪና የዉስጥ ሃይሎች ጅምር ጥረቱን ለማኮላሸት ሲባዝኑ ይስተዋላሉ። ይህም በቅርቡ በተካሄደዉ አንዳንድ የአህባሽ የስልጠና መድረኮች ሳዑዲ አረቢያን የማዉገዝ አዝማሚያ በማንፀባረቅ የተገለፀ እዉነታ በመሆኑ ጉዳዩ እንደገና መጤን እንደሚገባዉ አመላክቷል።
“አላዋቂ ሳሚ……….ይለቀልቃል”
ከዚሁ ወቅታዊ አጀንዳ ጋር ተያያዥ ነጥብ ላንሳ …በማህበረ ቅዱሳን ሐመር መፅሄት ጥር 2002 ዳንኤል ክብረት በ1991 “አክራሪ እስልምናና ለኢትዮጵያ ያለዉ አደጋ ” እንዲሁም “አክራሪ እስልምናና የኢትዮዽያ ቤተክርስቲያን አስቸጋሪ ፈተና” በሚል በ1999 የፃፈዉ ፤ኤፍሬም እሸቱ እ.ኤ.አ ‹‹እስልምናና አክራሪነት በክርስቲያን ደሴት ኢትዮጵያ ላይ ያለዉ አደጋ›› በሚል በ2008 ከአሜሪካ የፃፈዉ ፤ አባ ሳሙኤል ‹‹የሃይማኖት መቻቻል አለ የለም?›› በሚል ርዕስ በዝክረ ዘመን መፅሄት ላይ በ2000 ያሰፈሩት ፅሁፍ እና ሌሎችም መሰል ፅሁፎች ጀርባ ያሉት አንድምታዎች ሲታዩ ለሀገርና ለህዝብ የማይበጁ ከመሆናቸውም በላይ የእርስ በእርስ መቻቻልንና መከባበርን የሚያጠለሹ ይዘቶች እንዳሏቸዉ እንረዳለን። ለዛሬዉም ወቅታዊ አደጋ ደጋፊና መንስኤ የሆኑት እነዚሁ የፀሃፍቱ መረጃዎች በትክክለኛ መረጃ ላይ አለመመስረታቸዉ እንዳለ ሆኖ ለኛ ለኢትዮጵያዉያን ህዝቦች የሃይማኖት መቻቻል እና መከባበር የማይፈይዱ የመሆናቸዉ ጉዳይ ጎልቶ ይታያል። በአጠቃላይ እስልምና ተግባሩ ከቁርኣንና ከሃዲስ በማያወላዳ መንገድ የተቀዳና ተፈፃሚነቱም ይህንኑ የተከተለ መሆኑ እየታወቀ፤ በዚህ መርህ መሰረት የአምልኮ፣ የአለባበስና ሌሎችም የህይወት እንቅስቃሴያቸውን የሚያደርጉትን ሙስሊሞች “ወሃብያ” በሚል መፈረጅ አግባብ ካለመሆኑም በላይ የሃይማኖት ነፃነትን መጋፋትና ሳይደርሱ መድረስን ያነገበ ሰላም አደፍራሽ አስተሳሰብ ነው። አደገኛ አስተሳሰብ! ኺዋሪጅ፣ አልቃኢዳና ወሃብያን አቀላቅሎና ትርጉማቸውን አዛብቶ የሚካሄደው ፍረጃ ህዝበ ሙስሊሙ አንድነቱን ለመበጥበጥና ለመበጣጠስ ያቀዱ ዕኩይ ኅይሎችን ተልዕኮ ከመስበክ ያለፈ ፋይዳና አሳማኝ ምክኒያት የለውም። ለዚህም ነዉ “አላዋቂ ሳሚ… ይለቀልቃል” ያልኩት።
ምን ይጠበቅብናል?
መላዉ ኢትዮጵያዊ ሙስሊም ማህበረሰብ ጥንትም ሆነ ዛሬ ከማንም ጋር ጠብ የለዉም። ከሃይማኖት ተቋምም ጋር ቁርሾ የለዉም።ሊኖረዉም አይችልም። ከመንግስትም ጋር እንዲሁ! የኢህአዴግ መንግስት ሃይማኖቱን እንዲያራምድ ሕገመንግስታዊ ነፃነትና መብትን አጎናፅፎታል። ባህሉን፣ ልምዱን፣ ወጉን ኢስላማዊ መገለጫዎቹን እና ቅርሶቹን ተንከባክቦ እንዲይዝ ፣እንዲያቆይና ለትዉልድ እንዲያስተላልፍ ብሎም ለዓለም ማህበረሰብ እንዲያስተዋዉቅ ዕድሉንና መብቱን ሰጥቶታል ። ይህም ህገመንግስታዊ ዋስትናን አግኝቷል። የዜግነት ክብሩንና መብቱን ከሃይማኖት ነፃነቱ ጋር አረጋግጧል። እናም የኢህአዴግ ጠላት ሊሆን አይችልም። ይልቁንም ከገዢዉ ፓርቲ (መንግስት) ጋር ተባባብሮ በጋራ አገራዊ ጉዳዩች ላይ እንደ ዜጋ የሚጠበቅበትን ድርሻ በላቀ ደረጃ እይተወጣ ይገኛል ። ይህ ህዝበ ሙስሊሙ ከመንግስት ጋር ያለዉ መልካም ግንኙነት ወደ ላቀ ምዕራፍ እንዳይሸጋገር የሚያደናቅፉ ሃይሎችን ግን መንግስት በበሳል አመራር እና ዉሳኔ አሰጣጥ ልምዱ እንዲከታተላቸዉ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚኖረው ሙስሊም በአፅንኦት እየጠየቀ ይገኛል። እንደሌሎች እምነት ተከታይ የአገሪቱ ዜጎች ሁሉ ለሙስሊሙ ማህበረሰብ በህገመንግስታዊ ስርአቱ የተሰጠዉን መብት መጠቀም ብቻ ሳይሆን፤ ሙስሊሙ ይህንን ያረጋገጠለትን ህገመንግስታዊ ስረዓት ይጠብቀዋል። ይንከባከበዋል። ህገመንግስታዊ ስርአቱን በማክበርና በማስከበር ሂደቱም ከመንግስት ጎን ይሰለፋል። ይህንኑ ባለፉት ሁለት አስርት አመታት አሳይቷል። ወደፊትም በዚሁ አቋም ከመንግስት እና ከህገመንግስታዊ ስርአቱ ህልዉና መጠበቅ ጋር ለመራመድ የሚተጋዉ ሙስሊም ማህበረሰብ ግን በሃይማኖቱ ጉዳይ ላይ የማንንም ጣልቃ ገብነት አይሻም። በህገመንግስቱ ከተደነገገዉ ዉጪ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን ይቃወማል። መንግስት በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ወይም በሌሎች የዉጪና የዉስጥ ሃይሎች አለያም በፀረ-ኢስላም አቋም ላይ በሚገኙ ወገኖች ግፊት ወይም ጫና በሙስሊሙ ማህበረሰብ መንፈሳዊ አጀንዳ ዉስጥ ሊገባ አይገባዉም። በቅርቡ በአንዳንድ የመንግስት አስፈፃሚ አካላት ግን ሲገባ ተስተዉሏል። ይህ ሁኔታ ታዲያ በአገር ዉስጥም ሆነ በዉጪ የሚገኙ ኢትዪጵያዉያን ሙስሊሞችን ቅር ማሰኘቱ አልቀረም ። ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ አሁንም መንግስታችን ሁኔታዉን በሰከነ መንገድ በማየት እንዲመረምረዉና መፍትሄ እንዲሻለት ፍፁም ሰላማዊ ጥያቄዉን ለመንግስታች በተለያየ መንገድ እያቀረበ ይገኛል።
ከሁሉም በላይ አገራችን ኢትዮጵያ በታሪክ ያላትን ክብር በተለይም ከዓረቡ አለም ጋር ያላትን የቆየ ታሪካዊ ግንኙነት ይህ ክስተት እንዳያጠለሸዉ ይሰጋል። ዛሬ የዓረቡ ዓለም “የዓለም 1 ነጥብ 6 ቢሊዮን ሙሰሊሞች ለሃገራችን ህዝቦች ባለዕዳ ናቸዉ” እስከማለት በደረሱበት ወቅት ከ1433 ዓመታት በፊት መቀበሏ በዓለም እስልምና በነፃነት የኖረባትን ታሪካዊ ማዕረግና የመልካም እሴት ተምሳሌትነቷን የሚፈታተን አደጋ እንዳያጋጥም የብዙዎች ስጋት ነዉ፡፡ 50 ሺ አባላትን ከመላዉ አለም ያሰባሰበዉ ዓለም አቀፍ ሙስሊም ማህበረሰብ የአብደላ አልሃሪሪ የአህባሽ አመለካከት ከእስልምና መስረታዊ ህግጋት ጋር የሚጋጭ በመሆኑ ዉድቅ ካደረገዉ ሰነባብቷል። ይህ ቡድን ግን ኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞችን በአስተሳሰቡና አመለካከቱ ለማጥመቅ ፈቃድ አግኝቷል። እዚህ ላይ ቡድኑ ለምን ገባ አደልም ጥያቄዉ፤ “መጅሊስ ከመንግስት ጋር ተባብሮ ቡድኑ ስልጠና እንዲሰጥ ሁኔታዎች ለምን ተመቻቹለት?” ፤ “ይህን አመለካከት ለምን ተቀበሉ እንባላለን?፣ ህዝበ ሙስሊሙ ድህነትና ኋላቀርነት ከመንግስት ጋር ተባብሮ ለማስወገድ እየተጋ ባለበት ወቅት አንድነቱን የሚከፋፍል አመለካከት ካልተቀበልክ ለምን ይባላል?” የሚለው ነው የብዙዎቹ መሰረታዊ ጥያቄ! እናም መንግስትና ህዝበ ሙስሊሙን ለማራራቅ የሚሯሯጡ ሃይሎች ከእኩይ ድርጊታቸዉ ይታቀቡ ዘንድ የመንግስትን ትብብር እየጠየቁ የሚገኙት የብዙሃኑ ህዝበ ሙስሊሞች ጥያቄ ፍትሃዊና ፈጣን ምላሽ ከመንግስታችን እንደሚሰጠው ተስፋ በማድረግ ፅሁፌን እቋጫለሁ። ቸር ያሰማን፤ ሰላም!

